Friday, 5 January 2024

የነቢያት ናፍቆት ተወለደ

 

በዲያቆን ያሬድ መለሰ

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት የብዙ አበው ነቢያት ናፍቆትና ምኞት ነበር። ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን የነቢያት ናፍቆት የሚዘክር ሥርዓተ አምልኮ አላት። የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ በተለይም ከጌታችን ልደት አስቀድሞ ያሉ ሦስቱን የእሑድ ሳምንታትን ስብከት፣ብርሃን፣ኖላዊ ብሎ ሰይሞልናል። በእያንዳንዱ እሑድ ባለው መዝሙር የክርስቶስን መወለድ ነቢያቱ እንዴት ይናፍቁ እንደነበር እናዜማለን። የእነርሱ ስብከታቸው ብርሃናቸው ጠባቂያቸው አዳኛቸው መሆኑን እንመሰክራለን። ከጌታችን ልደትም አስቀድሞ ይህንን እያሰብናና እየዘከርን የነቢያቱን ጾም እንጾማለን። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ ነበር” (ዕብ. ፩፥፩) እንዳለ የተነበዩትን ትንቢት መሰሉትን ምሳሌ እናስባለን። ቅዱስ ጴጥሮስም “... በቅዱሳን ነቢያትም ቀድሞ የተባለውን ቃል በሐዋርያቶቻችሁም ያገኛችኋትን የጌታንና የመድኃኒትን ትእዛዝ እንድታስቡ በሁለቱ እያሳሰብኋችሁ ቅን ልቡናችሁን አነቃቃለሁ።” (2 ጴጥ. ፫፥፩-፪) እንዳለ በነቢያቱ ቀድሞ የተባለውን ቃል እያሰብን የጌታችንን መወለድ የነቢያቱ ናፍቆትና ጉጉታቸው መፈጸሙን እያሰብን እናመሰግናለን።

የነቢያት ናፍቆት

አዳምና ሔዋን ከገነት ከተባረሩበት ጊዜ ጀምሮ የሰው ልጆች ወደ ዓለም የሚመጣውን አዳኝ ይጠባበቃሉ ይህም የአባቶችን ኃጢአት ብቻ ሳይሆን የሰውን ሁሉ ኃጢአት የሚቤዥና ሰዎችን ሁሉ ከኃጢአት ከፍትወትና ከሞት ባርነት ነጻ የሚያደርግ የሰዎች እምነትና ተስፋ ጌታ ለእነርሱ በገባው ቃል ላይ የተመሠረተ ነበር። በብሉይ ኪዳንም ሁሉ (ማለትም ከክርስቶስ መምጣት በፊት) ነቢያት የተመረጡት ሰዎች መካከል ብቅ አሉ፣ በእርሱም እግዚአብሔር እስራኤላዊያን የእምነትን ንጽሕና መጠበቅና አዳኛቸውን ለመቀበል ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው አሳስቧቸዋል።

አዳምና ሔዋንን ከገነት ባወጣቸው ጊዜ የመጀመሪያው የአዳኙን የወደፊት ልደት በተመለከተ የመጀመሪያው ቃል የተናገረው እግዚአብሔር ራሱ ነው። ላሳታቸው እባቡ በተናገረው ቃል እንዲህ አለ፦"በአንተና በሴቲቱ መካከል፥ በዘርህና በዘርዋም መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ። እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኮናውን ትቀጠቅጣለህ” (ዘፍ ፫፡፲፭) ። በቤተክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት በዚህ ትንቢት ውስጥ ያለው እባብ የወደቀውን እግዚአብሔር መልአክን ይወክላል እሱም ዲያብሎስ ነው። ሴቲቷ (ገላ. ፬፥፬) ወደፊቱን አዳኝን በምትወልድ ድንግል ትመሰላለች።

አባታችን አብርሃም " በማዋዕልየኑ ትፌኑ ወልድከ ወሚመ ታርእየኒ ኪያሃ ዕለተ" ብሎ ይህን እኛ ያየነውን ዕለት ናፈቀ። ከምሳሌው በቀር እንደማያይ "አኮ ዘአርእየከ ኪያሃ አላ አምሳሊሃ ዕድዎ ለዮርዳኖስ ወትረክቦ ለመልከ ጼዴቅ" አለው። መልከ ጼዴቅም ኅብስተ አኮቴት ጽዋ በረከት ይዞ ተቀበለው ይህን ባየ ጊዜ የብዙኃን አባት የተባለ አብርሃም እጅግ ደስ አለው። (ዘፍ. ፲፬፥፲8)

ስለጌታችን ወደ ዓለም መምጣት የሚናገረው ትንቢት እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባው ቃል ኪዳንም አለ። እግዚአብሔር አምላካችን የአብርሃምን እምነት ከፈተነ በኋላ፣ እንዲህ አለ፡-“ቃሌን ሰምተሃልና የምድር አሕዛብ ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ” (ዘፍ. @2፡፲8) ። ቤተክርስቲያን እነዚህ ቃላት መሲሑ የአብርሃም ዘር መሆኑን የሚያመላክት ትንቢት እንደሆነ ታስተምራለች።

በዘፍጥረት መጽሐፍ መጨረሻ ላይ ስለ ክርስቶስ ልደት ሌላ ምሥጢራዊ ትንቢት አለ። ጻድቁ ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ለልጆቹ ከተናገራቸው ትንቢቶች በአንዱ ውስጥ የሚከተለው ቃል ነበረ። "በትረ መንግሥት ከይሁዳ አይጠፋም፥ ገዥ ዘንግም ከእግሮቹ መካከል፥ ገዥ እስኪመጣ ድረስ። የአእዛብ መታዘዝም ለእርሱ ይሆናል” (ዘፍ. $9፡፲) ። በዚህ የመጽሐፍ ክፍለ ንባብ ገዥ የተባለም ክርስቶስ ነው።

ነቢዩ ሚክያስም ክርስቶስ ከመወለዱ 700 ዓመታት በፊት የኖረ ቢሆንም ስለ መሲሑ የወደፊት መምጣት ተናግሯል። "አንቺ ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ታናሽ ነሽ፥ ከአንቺ ግን በእስራኤል ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል፥ አወጣጡም ከጥንት ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ ከአንቺ ግን ወደ እኔ ይወጣል" (ሚክ. ፭፡2) እዚህ ላይ የክርስቶስ የልደት ቦታ ቤተልሔም እንደሆነች እናያለን። (ማቴ. 2፥፭-6)

ነቢዩ ኢሳይያስ፣ ከነቢዩ ሚክያስ ጋር በተመሳሳይ ጊዜ ስለ ክርስቶስ መወለድ በርካታ ትንቢቶችን ትቶ ነበር። "ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፥ ከሥሩም ቅርንጫፍ ይበቅላል። የእግዚአብሔር መንፈስ፣ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ፣ የምክርና የኀይል መንፈስ፣ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ያርፍበታል፤ በዚያም ቀን የእሴይ ሥር ይሆናል፤ እርሱም ያድናል። ለሕዝብ ባንዲራ ቁሙ; አሕዛብ ይፈልጉታልና፥ ማረፊያውም በክብር ትሆናለች” (ኢሳ. ፲፩፡፩-፲) ። ከእሴይና ከዳዊት ነገድ ከድንግል ይወለድ እንዳለው እንዲሁም በትንቢቱ ሁለተኛ ክፍል ወደ ክርስቶስ የሚመለሱትን አእዛብን ይጠቅሳል።(ማቴ. ፩፥፭-6)


ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ስለጌታችን መወለድ ትንቢት እንደተናገረ "ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፡ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች" (ኢሳ 7፡፲፬)

ሌላው የኢሳይያስ ትንቢት ስለ ክርስቶስ የወደፊት ልደት፣ተአምራት፣ ጥንካሬ፣ መንፈሳዊ ኃይል እና ፈውሶች ተናግሯል በዚህም ምክንያት የኢሳይያስ የትንቢት መጽሐፍ ደረቅ ሐዲስ ይባላል። በትንቢቱ እንዲህም አለ፡-"አምላክህ መጥቶ ያድንሃል። በዚያን ጊዜ የዕውሮች ዓይኖች ይገለጣሉ የደንቆሮችም ጆሮ ይከፈታል። የዚያን ጊዜ አንካሶች እንደ ሚዳቋ ይዘልላሉ የዲዳም ምላስ ይዘምራል።” (ኢሳ. #፭፡፬-6) ። "ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፡ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች" (ኢሳ 7፡፲፬) ። ይህም ትንቢት ስለ መሲሑ መምጣት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ሥጋ የመገለጥ ምስጢርም ያስረዳል።

ነቢየ እግዚአብሔር ልበ አምላክ ክቡር ዳዊትም "ፈኑ እዴከ እምአርያም፤አድኅነኒ ወባልሐኒ እማይ ብዙኅ፤ ወእምእዴሆሙ ለደቂቀ ነኪር።" እጅህን ከአርያም ላክ፤ ከብዙ ውኃም አድነኝ፤ ከባዕድ ልጆችም አድነኝ። (መዝ. ፻፵፫፥፯) ከአርያም እጅህን ላክ እያለ በምሥጢር የክርስቶስን መምጣት ሲጠባበቁ ኖረዋል። ዳግመኛም ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚመራ ብርሃን ወደ ዓለም እንዲመጣ “ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ” (መዝ $2፡፫) በማለት ተናግሯል፡፡ ይህም ብርሃን፣ ጽድቅ፣ እውነት የሆነውን ልጅህን (ወልድን) ላክልን፤ እርሱ መርቶ ወደ መንግሥተ ሰማያት ያስገባን ዘንድ በማለት ተማጽነዋል።

ስለ አዳኝ መወለድ እና ቦታ ከተነገሩት በርካታ ትንቢቶች ባሻገር፣ በብሉይ ኪዳን ውስጥ የእርሱ ምድራዊ መንገድ፣ ተአምራት፣ መከራ፣ የመስቀል ሞት እና ትንሳኤ ጨምሮ ሌሎች ብዙ ትንቢቶች አሉ።

የነቢያቱ እምነትና መታመን

በእርግጥ ልደት የነቢያት ናፍቆት መሆኑን ለማስገንዘብ ጥቂቱን ትንቢት አነሳሳን እንጂ ስለጌታችን መምጣት የተነገሩ የትንቢት ክፍሎች ከላይ የጠቀስናቸው ብቻ አይደሉም። ነቢያቱ ግን በትንቢቱና በምሳሌውም ደስ ይላቸው ነበር። እኛ ያየነውን መገለጥ ቢያዩ እንዴት ደስ ይለው ይሆን? አብርሃም መልከ ጼድቅን ዐይቶ ደስ እንዳለው ክርስቶስን ቢያይ በኅብስተ በረከት ጽዋ አኮቴት ደስ እንዳለው በክርስቶስን ሥጋና ደም ቢያይ ምንኛ ይደነቅ ይሆን?

በትንቢቱና ምሳሌው በተስፋው ለጌታ የታመኑ በዚህ ዘመን ቢሆን እንዴት ያገለግሉት ይሆን?

ለዚህም ነው ጌታችን "እናንተ የሚታዩትን ያዩ ዘንድ ብዙ ነቢያት ፈለጉ አላዩም እናንተ የምትሰሙትንም ይሰሙ ዘንድ ፈለጉ አልሰሙም ያዩ ዓይኖቻቹ የሰሙ ጆሮዎቻችሁ ብጽአን ናቸው" (ማቴ. ፲፫፥፲6-፲7) እንዳለ የነቢያትን ናፍቆት ማየት መታደል ነው። ስለዚህም በዚህ ዘመን ነቢያቱን መሻት ያየን ሁሉ በብዙ(አብልጠን) ለጌታችን መታመን በእርግጥ ይገባናል።

 

ከልደተ እግዚእ በረከት ይክፈለን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

No comments:

Post a Comment