Friday, 17 April 2026

ከጾም በኋላ፦ ከቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የተሰጠ ምክር

ወዳጆቼ ሆይ! ምንም እንኳን የጾሙ ወቅት ቢያልፍም፣ ፈርኀ እግዚአብሔር ግን በእናንተ ዘንድ ጸንቶ ይኑር፤ ምንም እንኳን የተቀደሰው የዐቢይ ጾም ጊዜ ቢፈጸምም፣ መታሰቢያውን ግን ከአእምሯችን አናውጣው። ለዚህ ማሳሰቢያ ማንም ሰው ቅሬታ አይሰማው፤ ይህን የምላችሁ ሌላ የጾም ወቅት ልጭንባችሁ ፈልጌ አይደለም፤ ነገር ግን እንድታርፉና አሁን ደግሞ እውነተኛውንና ይበልጥ ጥንቁቅ የሆነውን ጾም እንድታሳዩ ስለተመኘሁ ነው እንጂ። ምክንያቱም አንድ ሰው ሳይጾም ሊጾም ይችላል። ይህ እንዴት ይሆናል? እኔ እነግራችኋለሁ፤ በአንድ በኩል ምግብን እየተመገብን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከኃጢአት እንራቅ። እኛን የሚጠቅመን ጾም ይህ ነውና፤ በጎነትን በቀላሉ መፈጸም እንድንችል፣ ከምግብ የምንከለከለውም ይህንኑ ጾም በዓላማ ይዘን ነው። ስለዚህ ለሥጋችን ተገቢውን ጥንቃቄ ለማድረግና ነፍሳችንንም ከኃጢአት ነጻ አድርገን ለመጠበቅ ከፈለግን እንጠንቀቅ እንዲሁም በዚያው መሠረት እንኑር።

 

ይህ የጾም መንገድ ለእኛ ይበልጥ ቀላል ይሆንልናል። ስለ ሌላኛው ዓይነት ጾም፣ ማለትም ከምግብ ስለ መከልከል፣ ብዙዎች የራብን ሸክም መሸከም ከብዶናል ሲሉ፣ የሰውነታቸውን መድከም ሲያማርሩ፣ እንዲሁም ያለ ገላ መታጠብና መጠጣቸውንም በውኃ ላይ ብቻ መገደባቸው ጤናቸውን እያበላሸው እንደሆነ በመናገር ብዙ መራራ እሮሮዎችን ሲያሰሙ እሰማ ነበር። ከኃጢአት በመጾም ረገድ ግን እንዲህ ያለ ሰበብ ሊኖር አይችልም። እነዚህን ነገሮች ሁሉ እየተጠቀሙ ለሥጋ የሚያስፈልገውን አገልግሎት መስጠት፣ በተመሳሳይ ጊዜም ለነፍስ ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ ይቻላል። በእውነቱ አሁን ከእነዚህ ነገሮች እንድትከለከሉ እየገፋፋኋችሁ አይደለም። ከኃጢአት ብቻ ራቁ፣ በዚያም ራስን የመግዛት ጽናት ዘወትር ታማኝ ሆናችሁ ተገኙ። በዚህ መንገድ በማንኛውም የሕይወት ዘመናችሁ እውነተኛውን ጾም መለማመድ ትችላላችሁ። እኔ የዘረዘርኳቸውን ነገሮች በመጠን ከመጠቀም የሚያግዳችሁ ምንም ነገር የለም፤ ነገር ግን በማንኛውም መልኩ ኃጢአት የተከለከለ ነው። ሆኖም ኃጢአት የሚወለደው በትክክልም እንደ ግብረ-ገብነት ማጣት፣ ሆድ አምላኪነትና ከመጠን በላይ ከሆነ ስንፍና ነው። ስለዚህ፣ እነዚህ ስህተት መሆናቸውን በግልጽ ስለምናውቅ፣ እያረፍን ነው በሚል ሰበብ ስህተት የሆነውን ነገር አንጠቀም ዘንድ አጥብቄ እመክራለሁ።

ከዚህ በፊት ደጋግሜ የተናገርኩትን አሁንም እንደገና እላለሁ፤ ምግብን በመጠኑ መጠቀም ለሥጋ ጤንነትም ሆነ ለነፍስ ሁኔታ በእጅጉ እንደሚጠቅም ሁሉ፣ በአንጻሩ ደግሞ ምግብን ያለአግባብ ማብዛት ሥጋንና ነፍስን፣ ሙሉውን ሰው ያበላሻል። በመብልና በመጠጥ ከመጠን በላይ መሆን የሥጋን ጥንካሬ ያደክማል፣ የነፍስንም ጤና ያጠፋል። ስለዚህ፣ ከልክ ያለፈ ፍላጎትን እንሽሽ፣ በገዛ ደኅንነታችንም ጉዳይ ቸልተኞች አንሁን፤ ከልክ ማለፍ የክፉ ነገር ሁሉ ሥር መሆኑን ስለምናውቅ፣ ቆርጠን ለመጣል እንጠንቀቅ። እያንዳንዱ የኃጢአት ቅርጽ እንደ ምንጭ ከሥጋዊ ምኞት ይፈልቃል። እነዚህ ክፉ አመሎች፣ ማገዶ እሳትን እንደሚያነድድ ሁሉ እኛንም ወደ ኃጢአት ያንሸራትቱናል። በእሳት ረገድ፣ የማገዶ መብዛት እሳቱን ያጎርሰዋል፣ ነበልባሉንም ወደ ላይ ከፍ ያደርገዋል። እዚህም እንዲሁ ነው፤ ራሳችንን ለቅንጦትና ለስካር አሳልፈን ከሰጠን፣ የሚነድደውን የኃጢአታችንን ክምር እናሰፋዋለን።

 በረከቱ ይደርብን

ምንጭ፦

  •     St. John Chrysostom, St. John Chrysostom: Baptismal Instructions, "The Fifth Instruction," (Mahwah, NJ: Paulist Press, 1963), pp. 80-81.

 

Thursday, 16 April 2026

ሞትና ትንሣኤ፡ ከውድቀት ወደ ዘለዓለም ሕይወት


በቀሲስ ያሬድ መለሰ

በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ እንደ ሞት የሚያስፈራና እንደ ትንሣኤ ደግሞ ተስፋ የሚሰጥ ነገር የለም። ሞት በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ጥያቄ ሆኖ የኖረ ምስጢር ሲሆን፣ ትንሣኤ ደግሞ ያንን ምስጢር የፈታ የድል አዋጅ ነው።

ሞትበሰው ልጅ የሕይወት ጉዞ መካከል እንደ ወጥመድ የተዘረጋ፣ በሥጋና በነፍስ መካከል ያለውን ስስ ክር የሚበጥስ፣ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ማክተሚያ የሚመስል ክስተት ነው። ከጥንት ፈላስፎች አንስቶ እስከ ዛሬው ሳይንቲስት ድረስ ሰው ሁሉ በዚህጥቁር መጋረጃፊት ቆሞ ተንቀጥቅጧል። ለአንዳንዶች ሞት የሁሉም ነገር ማብቂያ፣ የሕልውና መክሰሚያና የማይሻገር የጨለማ ግድግዳ ነው። በሰው ልጅ ሕይወት መሃል እንደ ድንገተኛ እንግዳ ገብቶ ውበትን የሚያረግፍ፣ ኃይልን የሚያደክም፣ የፍቅርን ጥሪ በዝምታ የሚሰርዝ ግዙፍ ምስጢር ነው።

የሞት ፍትሐዊነትና ሁሉን ወሳጅነት

ሞት በዚህ ምድር ላይ ካሉ ነገሮች ሁሉ እጅግፍትሐዊየሚመስል አድሎ የሌለበት ኃይል ነው። የሀብታሙን ቅጥር ግቢ ጥሶ እንደሚገባ ሁሉ የድሃውን ጎጆ ማንኳኳት አይዘነጋም። የኃያላንን ሰይፍ ሰብሮ፣ የነገሥታትን ዘውድ አውርዶ፣ የሊቃውንትን ጥበብ አጥፍቶ ሁሉንም እኩል ከአፈር ይደባለቃል። ሞት ለዕድሜ አይራራም፣ ለውበት አይሰስትም፣ ለሥልጣን አይንበረከክም። ሕፃኑን ከእናቱ እቅፍ፣ ወጣቱን ከሕልሙ ሜዳ፣ ሽማግሌውን ከምርኩዙ ላይ ነጥቆ የሚወስድ ሁሉን ወሳጅ ኃይል ነው። በዚህ ዓለም አደባባይ ላይ ማንም አምልጦት የማያውቅ፣ ሁሉንም ወደ አንዲት ጠባብ መቃብር የሚሰበስብ የግዴታ ጥሪ ነው።

ነገር ግን፣ ይህ አስፈሪ ጥያቄና ሁሉን አሸናፊ የመሰለው የሞት ኃይል በታሪክ አደባባይ ላይ ብቸኛና ፍጹም ምላሽ አግኝቷል። እሱም ትንሣኤ ነው።

ትንሣኤየሞትን ኃይል የሰበረ፣ ያንን የማይሻገር የመሰለውን የጨለማ ግድግዳ ወደ ሰማያዊ በርነት የለወጠ የድል ዜማ ነው። ሞት ጥያቄ ከሆነ፣ ትንሣኤ መልስ ነው። ሞት ሐዘን ከሆነ፣ ትንሣኤ የዘለዓለም ደስታ ነው። በክርስቶስ ትንሣኤ አማካኝነት ሞት መውጊያው ተሰብሮ፣ ትዕቢቱ ተንቆ፣ በሕይወት ብርሃን ተውጧል። ትንሣኤ ማለት የሰው ልጅ ከውድቀት አፈር ተነስቶ የከበረውን የዘለዓለም ሕይወት ልብስ የለበሰበት፣ ሞትም በመቃብር ድንጋይ ስር ለዘላለም የተሸነፈበት ታላቅ አዋጅ ነው። ስለዚህ ዛሬ ሞት ለእኛ መድረሻ ሳይሆን መሻገሪያ፣ መጨረሻ ሳይሆን የአዲስ ሕይወት መጀመሪያ ሆኗል። ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ ድል መንሳትህ የት አለ?” የሚለው የድል መዝሙር የሰው ልጅ ሁሉ የዘላለም ተስፋ ነው።


 

ሞት ለምን መጣ? ለምንስ አልጠፋም?

የሰው ልጅ ሕልውና በምድር ላይ ሲመሠረት የሕይወት እንጂ የሞት ዕጣ ፈንታ አልነበረውም። ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚያስተምረንየኃጢአት ደመወዝ ሞት ነው” (ሮሜ 623) ሞት ወደዚህች ዓለም የገባው እንደ እንግዳ ቢሆንም፣ በሰው ልጅ አለመታዘዝ ምክንያት የሰውነት ባሕርይ ላይ እንደ ሰፈረ ዝገት ሆነ። ሞት የተፈጥሮ ሕግ ሳይሆን የውድቀት ውጤት ነው፤ ሰው የሕይወት ምንጭ ከሆነው ከእግዚአብሔር በመለየቱ የመጣ የባሕርይ መዛባት ነው።

ይሁን እንጂ፣ ክርስቶስ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነትና በትንሣኤው ሞትን ድል አድርጎ ሳለለምን ሞት አሁንም ይቀጥላል? ለምንስ ወዲያው አልጠፋም?” የሚለው ጥያቄ የብዙዎች አእምሮ ውስጥ የሚመላለስ ጥልቅ ምስጢር ነው።

ታላቁ የቤተክርስቲያን አባት ቅዱስ አትናቴዎስ በታዋቂውበእንተ ሥጋዌ” (On the Incarnation) መጽሐፉ ላይ እንደሚገልጸው፣ ክርስቶስ ሞትን የገደለው በመሞት ነው።  ሕይወት የሆነው አምላክ ወደ ሞት ግዛት ዝቅ ብሎ በመውረድ ሞትን ከውስጥ በላው። አሁን በዓይነ ሥጋ የምናየው ሞት ኃይሉ የተሰበረ፣ መውጊያው የተሰባበረ፣ ጥርሱ የረገፈአንበሳነው። ሞት አሁንም በምድር ላይ ቢመላለስም፣ ለእኛ ግንመጥፋት” (Extinction) መሆኑ አብቅቷል። ይልቁንም ከአላፊው ዓለም ወደ ማላለፈው፣ ከምድራዊው ወደ ሰማያዊው ክብር የምንሻገርበትድልድይሆኖ ተቀይሯል። የሞት ትርጉም ከቅጣትነት ወደ ዕረፍት ተለውጧል።

ሞት ባይኖር ምን ይፈጠር ነበር?

ሥጋዊ ሞት ወዲያው የማይጠፋበት ምክንያት እጅግ የሚደንቅ መለኮታዊ ጥበብ አለበት። ሞት ባይኖር ኖሮ፣ ሰው በዚህች በበሰበሰችና በረከሰች ዓለም ውስጥ በኃጢአቱ እንደጸና ለዘለዓለም በኖረ ነበር። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙ እንደገለጸው፣ ሞት እንዲኖር የተፈቀደውክፋት ለዘለዓለም እንዳይኖርነው። ሞት ባይኖር ኖሮ ክፋት ገደብ አይኖረውም ነበር፤ የሰው ልጅም በበሽታ፣ በስቃይና በሥጋዊ ድካም እየማቀቀ ለዘለዓለም በምድር ላይ መኖሩ ምድርን ራሷን ማብቂያ ወደሌላት ሲኦል በለወጣት ነበር።

ሥጋዊ ሞት ያልጠፋው፣ በበሰበሰውና በማይበሰብሰዉ መካከል መለያ መስመር እንዲሆን ነው። አሁን ያለው ሥጋችን ከኃጢአት ጋር የተዋሐደ በመሆኑ፣ ይህ ሥጋ የግድ መፍረስና መበስበስ አለበት። እንደ አሮጌ ቤት ፈርሶ በአዲስና በማይበሰብስ የትንሣኤ አካል ለመታደስ ሞት ግድ ሆኗል። ስለዚህ ሞት ምንም እንኳን የኃጢአት ውጤት ቢሆንም፣ በውስጡ ግን የእግዚአብሔር ጥልቅ ምሕረት አለበት። ሞት ኃጢአት በሰው ባሕርይ ውስጥ እንዳይሰለጥን የሚያደርግመድኃኒትሆኖ ተሰጠ። ሰውን ከዚህ ከደካማና ከሚሰቃይ ሥጋ አሳርፎ፣ ወደማይበሰብሰውና ወደማያልፈው የትንሣኤ ሕይወት ለማዘጋጀት እንደ መሸጋገሪያ በር ሆነ። ሞት ለክርስቲያን ፍጻሜ ሳይሆን፣ የድሉ አክሊል የሚቀዳጅበት የሰማያዊው ቤት ደጃፍ ነው።

የክርስቶስ ትንሣኤና የእኛ ትንሣኤ

የክርስቶስ ትንሣኤ የታሪክ አጋጣሚ ሳይሆን የሰው ልጅ ተፈጥሮ የታደሰበት ታላቅ ክስተት ነው። እርሱ ሞትን ድል አድርጎ በመነሳቱ “የትንሣኤ በኵር” ተባለ። ልክ አንድ አዝመራ ሲደርስ መጀመሪያ የሚታጨደው ፍሬ የጠቅላላው ምርት ማሳያ እንደሚሆነው ሁሉ፣ የክርስቶስም ትንሣኤ ለሁላችንም ትንሣኤ ዋስትናና መመሪያ ሆነ። እርሱ የሞትን የብረት በሮች በመስበር፣ የሰው ልጅ ሁሉ በክብር የሚነሳበትንና ወደ ዘለዓለም ሕይወት የሚሸጋገርበትን ቀዳዳ መንገድ ቀደደ።

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ነገረ መለኮት እንደሚመሰክረው፣ የሰው ልጅ ሁሉ መነሳት (Universal Resurrection) የክርስቶስ ትንሣኤ ለፍጥረት ሁሉ ያበረከተው “ነፃ ስጦታ” ነው። ይህ ስጦታ በሰው እምነት ወይም በሥራ ጥራት ላይ የተመሠረተ ሳይሆን፣ ክርስቶስ የሰውን ባሕርይ ስለተዋሐደና ያንን ባሕርይ ይዞ ስለተነሳ ለሰው ዘር ሁሉ የተረፈ ጸጋ ነው። ስለዚህ አማኝም ይሁን ኢ-አማኝ፣ ጻድቅም ይሁን ኃጢአተኛ፣ ሁሉም በታላቁ ቀን ከመቃብር ይነሳሉ። ትንሣኤው የባሕርይ ግዴታ ነው፤ ሞት በሰው ዘር ላይ እንደሰለጠነ ሁሉ፣ ትንሣኤም በሁላችን ላይ ይሰለጥናል።

ሆኖም ግን፣ ሁሉም እኩል ቢነሱም የትንሣኤው ገጽታ ግን ይለያያል። መነሳት አንድ ቢሆንም፣ የሚነሱበት ክብርና የትንሣኤው ፍሬ ግን እንደየሰው አኗኗር ይወሰናል። ጌታችን በወንጌል እንዳስተማረው፦ “መልካም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ፣ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉ” (ዮሐ 5፡29) ።

ለጻድቃን ትንሣኤ ማለት የድካማቸው ማብቂያ፣ የአክሊላቸው መጀመሪያ፣ ከፈጣሪያቸው ጋር ፊት ለፊት የሚገናኙበት የብርሃን ወገግታ ነው። ለእነርሱ ትንሣኤው ሞቅ ያለና የሚያበራ እንደ ማለዳ ፀሐይ ነው። ለኃጢአታን ግን ትንሣኤው የኅሊናቸው ወቀሳ የሚሰማበት፣ የእግዚአብሔርን ፍቅር ባለመቀበላቸው ምክንያት የሚመጣ የፍርድ ትንሣኤ ይሆናል።

ስለዚህ የክርስቶስ ትንሣኤ ለሁላችንም የተሰጠ አዲስ የሕይወት ዕድል ቢሆንም፣ ትንሣኤያችን የደስታና የክብር እንዲሆን ዛሬውኑ በብርሃን ጎዳና መጓዝን ይጠይቃል። እርሱ ቀድሞ ተነሳ፤ እኛም በእርሱ ኃይል እንነሳለን—ይህ የክርስትና ተስፋ ማዕከልና የሰው ልጅ የመጨረሻው ድል ነው።

የሰው ልጅ በየትኛው አካል ይነሣል?

ይህ ጥያቄ ከጥንት ጀምሮ የሰውን ልጅ አእምሮ ሲያባንን የኖረ ትልቅ ምስጢር ነው። “የበሰበሰው ሥጋ፣ አፈር የሆነው አጥንት እንዴት ሊመለስ ይችላል? የምንነሳውስ በየትኛው ማንነታችን ነው?” የሚሉ ጥያቄዎች ይነሳሉ። ታላቁ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለዚህ ጥያቄ ሲመልስ፦ “የሚዘራው ፍጥረታዊ አካል ነው፣ የሚነሳው ግን መንፈሳዊ አካል ነው” (1ቆሮ 15፡44) ይላል።

እዚህ ላይ ልብ ሊባል የሚገባው መሠረታዊ እውነት አለ፤ የምንነሳው በሌላ አዲስ አካል ሳይሆን፣ በዚህ በራሳችን አካል ነው። ነገር ግን ይህ አካል በትንሣኤ ጊዜ ባሕርዩ ይለወጣል። አሁን ያለን አካል የሚራብ፣ የሚጠማ፣ የሚደክም፣ ለሕመም የሚገዛና በመጨረሻም የሚበሰብስ “ፍጥረታዊ አካል” ነው። በትንሣኤ የሚኖረን ግን ከእነዚህ ደካማ ባሕርያት ነፃ የሆነ “መንፈሳዊና የማይበሰብስ አካል” ነው።

የሰው ልጅ የትንሣኤ አካል የክርስቶስን የትንሣኤ አካል አምሳያ የሚከተል ሲሆን፣ ይህም በምስጢራዊ አንድነትረቂቅና ግዙፍሆኖ የሚገለጥ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሳ በኋላ፣ በተዘጋ በር በመግባትና በደቀ መዛሙርቱ መካከል በድንገት በመገኘት የባሕርይ ረቂቅነቱን አሳይቷል፤ በሌላ በኩል ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ በጣታቸው እንዲዳስሱትና እንዲያረጋግጡ በመፍቀድ፣ እንዲሁም አብሮአቸው በመብላት እውነተኛና ግዙፍ ሥጋ መሆኑን አረጋግጧል።

በዚሁ መሠረት፣ በትንሣኤ ዘጉባኤ ጊዜ የሰው ልጅ የሚነሣው አሁን ባለው ደካማና ለሕመም በሚጋለጥ ሥጋ ሳይሆን፣ በክብርና በብርሃን በተጎናጸፈ ማንነት ነው። ይህ አዲስ አካል ረሃብና ጥም የማይሰማው፣ እርጅናና ደዌ የማይስማሙት፣ እንዲሁም ማንኛውም ዓይነት የአካል ጉድለት የማይገኝበት ፍጹም አካል ይሆናል። ይህም የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን፣ የሚሞተውም የማይሞተውን ለብሶ በዘላለም ክብር የሚኖርበት ሰማያዊና መንፈሳዊ አካል ነው።

ይህ አካል እንደ መላእክት ረቂቅ ቢሆንም፣ የራሳችን መሆኑ ግን አይታበልም። በትናንትናው ድካማችን የተዘራው ማንነታችን፣ በነገው የትንሣኤ ክብር በማይጠፋ ድል ተጎናጽፎ ይነሳል።

የቀደሙ አባቶች እሳቤና ማጠቃለያ

የቤተክርስቲያን አባቶች የትንሣኤን ምስጢር ሲያበሩት እንደ ቀትር ፀሐይ ደምቀው ይታያሉ። ትንሣኤ ለእነርሱ የታሪክ ክስተት ብቻ ሳይሆን፣ ሞት ድል የተነሳበትና የሰው ልጅ ተፈጥሮ የታደሰበት የጽድቅ ጮራ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዚያ ዝነኛ የትንሣኤ ስብከቱ ላይ በድል አድራጊነት እንዲህ ይላል፦ "O Death, where is thy sting? O Hell, where is thy victory? Christ is risen, and thou art overthrown. Christ is risen, and the demons are fallen. Christ is risen, and the angels rejoice. Christ is risen, and life reigns. Christ is risen, and not one dead remains in the grave.""ሞት ሆይ! መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ! ድል መንሳትህ የት አለ? ክርስቶስ ተነሣ፤ አንተም ወደቅህ። ክርስቶስ ተነሣ፤ አጋንንት ወደቁ። ክርስቶስ ተነሣ፤ መላእክት ሐሴት አደረጉ። ክርስቶስ ተነሣ፤ ሕይወትም ነገሠ። በመቃብር ያለ አንድም ሙት የለም፤ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነስቷልና።" ይህ አዋጅ መቃብር የሕይወት እስር ቤት መሆኑ አብቅቶ የዘለዓለም ሕይወት መፍለቂያ መሆኑን ያበስራል።

ቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ በበኩሉ ክርስቶስንየሕይወት መገኛብሎ ይጠራዋል። ቅዱሱ ሲያስተምር "For as in Adam all die, even so in Christ shall all be made alive... Since He is the Life by nature, He made our nature to be life in Himself. He has become the first-fruits of them that slept, and the first-born from the dead, that He might subject all things to Himself and destroy the power of death." “በአዳም ሁሉም እንደሚሞቱ፣ እንዲሁ በክርስቶስ ሁሉም ሕያዋን ይሆናሉ... እርሱ በባሕርይ ሕይወት ስለሆነ፣ የእኛን ባሕርይ በራሱ ሕያው አደረገ። ሁሉን ነገር ለራሱ ያስገዛ ዘንድ፣ የሞትንም ኃይል ያጠፋ ዘንድ ላንቀላፉት በኵር፣ ከሙታንም የበኵር ልጅ ሆነ።” ይላል። ሞት የሰውን አካልና ነፍስ ለጊዜው ቢነጣጥልም፣ ክርስቶስ ግን በትንሣኤው ሁለቱን መልሶ በማይፋታ አንድነት አዋሕዷቸዋል። በዚህም መበስበስን ድል አድርጎ የሰውን ልጅ ወደ ቀደመ ክብሩ መለሰው።

ሌላው ታላቅ አባት ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ፣ ትንሣኤን የሞት ፍጹም ሽንፈት አድርጎ ይገልጸዋል። "Now that the Saviour has risen, death is no longer terrible, but all who believe in Christ tread it underfoot as nothing. For death has been swallowed up by Life, and the corruption of our nature has been clothed with immortality." “አሁን መድኃኒታችን ስለተነሣ፣ ሞት ከእንግዲህ አያስፈራም፤ በክርስቶስ የሚያምኑ ሁሉ እንደ ምንመን ቆጥረው ይረግጡታል። ሞት በሕይወት ተውጧልና፣ የተፈጥሯችንም መበስበስ አለመሞትን ለብሷል።” ቅዱሱ እንዳለ ክርስቶስ የሰውን ሥጋ ለብሶ በመካከላችን ባይኖርና በትንሣኤው ሞትን ባያሸንፈው ኖሮ፣ የሰው ልጅ ሁሉ በመቃብር በስብሶ በቀረ ነበር። አሁን ግን ሞት በጌታ ሥጋ ውስጥ በገባ ጊዜ እንደ ገለባ በእሳት ተቃጠለ። ይህም የሰው ልጅ የሞት ፍርሃት ተወግዶ በትንሣኤ ተስፋ እንዲሞላ አድርጎታል።

ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዝናዙ ደግሞ ትንሣኤን ከአማኙ ሕይወት ጋር በማቆራኘት ይተነትነዋል። "Yesterday I was crucified with Him; today I am glorified with Him. Yesterday I died with Him; today I am made alive with Him. Yesterday I was buried with Him; today I rise with Him." “ትላንት ከእርሱ ጋር ተሰቀልሁ፤ ዛሬ ከእርሱ ጋር ክብርን አገኛለሁ። ትላንት ከእርሱ ጋር ሞትሁ፤ ዛሬ ከእርሱ ጋር ሕያው እሆናለሁ። ትላንት ከእርሱ ጋር ተቀበርሁ፤ ዛሬ ከእርሱ ጋር ከመቃብር እነሳለሁ።” በማለት፣ ትንሣኤ በየቀኑ ከኃጢአት መቃብር የምንነሳበትና አዲስ ሕይወት የምንለብስበት ኃይል መሆኑን ያስገነዝባል። ሞት ለክርስቲያን ፍጻሜ ሳይሆን፣ ምድራዊውን የቤት ሥራ ጨርሶ ወደ ጌታ መግቢያ በር መሆኑን እነዚህ አባቶች በአንድ ልብ ይመሰክራሉ።

በመጨረሻም፣ በሰውነታችን መሃል የሚሰማው የሐዘን ስሜት በትንሣኤ ብርሃን ይሻራል። እምነታችን በባዶ መቃብር ላይ የቆመ ነው፤ ተስፋችንም ሞትን ድል በነሳው ጌታ ላይ የተመሠረተ ነው። ስለዚህ ዛሬ ሞትን የምናየው እንደ ጨካኝ ጠላት ሳይሆን፣ ወደ ዘለዓለም ክብራችን እንደሚሸኘን ታማኝ መንገድ ነው። ትንሣኤ መቃብርን ከተስፋ መቁረጥ ጉድጓድነት ወደ አዲስ ሕይወት መፍለቂያነት ቀይሮታል። በክርስቶስ ዘንድ የምድራዊው ጉዟችን ፍጻሜ፣ የማያልቀው የዘለዓለም ቀን መጀመርያ ነው።

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር  

ዋቢ ምንጮች፦

  •         ቅዱስ ቄርሎስ በሉቃስ ወንጌል ትርጓሜው ድርሳን 153 Commentary on the Gospel of Luke, Homily 153. 
  •    ቅዱስ አትናቴዎስ - በእንተ ሥጋዌ On the Incarnation of the Word, Paragraph 27.
  •  ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - የትንሣኤ ስብከት The Paschal Homily (Sermon) of St. John Chrysostom
  •  ቅዱስጎርጎርዮስዘእንዚናንዙ (St. Gregory Nazianzen) ቅዱስጎርጎርዮስዘእንዚናንዙ (St. Gregory Nazianzen) Oration 45: Second Oration on Easter (ሁለተኛውየፋሲካድርሳን)