በዲያቆን ያሬድ መለሰ
ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ ውስጥ ሰፊ ጊዜ ከሚታሰቡና ከሚዘከሩ ጉዳዩች መካከል አንዱ አስተርእዮ ነው።ዘመነ አስተርእዮ ሲያጥር ከጥር ፲፩ ቀን እስከ ጥር ፴፤ ሲረዝም ደግሞ ከጥር ፲፩ ቀን እስከ መጋቢት ፫ ቀን ይሆናል፡፡ በዚህም መሠረት ቀናቱ ሲያጥር ፳፤ ሲረዝም ፶፫ ይሆናሉ ማለት ነው። በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔርን መገለጥ በስፋት እናስባለን።
አስተርእዮ መታየት ወይም መገለጥ የሚል ትርጓሜ ያለው የግእዝ ቃል ነው፡፡በግሪክ ‹‹ኤጲፋኒ›› የሚል ስያሜ አለው። ቃሉ ሁለት መሠረታዊ ሃሳቦችን የያዘ ነው አንደኛው ቴዎፋኒ ሲሆን ሁለተኛው ኤጲፋኒ ነው። "ቴዎፋኒ(Theophany) የግሪክ ቃል ነው። 'ቴኦፋኒያ'፣ (ቴኦስ - አምላክ፣ ፋኔያ - መገለጥ) 'Theophania', (Theos - God; phaneia - manifestation) በጥሬ ትርጉም "የእግዚአብሔር መገለጥ" ማለት ነው። የኤጲፋኒ (ኤፒ - በላይ፣ ፊንያ - መገለጥ) ቀጥተኛ ትርጉሙ "ከላይ መገለጥ" (Manifestation from above) ነው። ሁለቱም ትርጉማቸው መገለጥ ቢሆንም በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያናችን ቴዎፋኒ የሚለውን ቃል የምንጠቀመው የጌታችንን በተጠመቀ ጊዜ የሥላሴን መገለጥ ለማስታወስ ነው። ኤጲፋኒ የሚለው ቃል ዘወትር የምንጠቀመው የኛን ሥጋ የመዋሐድ በዓላትን (ልደት፣ መገረዝ፣ ለቤተመቅደስ መቅረብ...ወዘተ) ሁሉ ለማስታወስ ነው።
የተገለጠ አምላክ (Revealed God)
መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት "እግዚአብሔር እግዚእ አስተርአየ ለነ” "እግዚአብሔር ጌታ ነው, ለእኛም ራሱን ገለጠ; በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው” (መዝ 117፡27፣26) ። ይህ ቀላል ግን ጥልቅ ሀረግ የክርስቲያን አስተምህሮ አስኳል ነው፡ እግዚአብሔር በእውነት ራሱን ገልጦልናል። ይህ ነው ክርስትናን ልዩ የሚያደርገው እና ከሁሉም ሰው ሰራሽ እምነቶች የሚለየን ነው። ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ መልእክቱ ላይ “በእኔ የተሰበከ ወንጌል እንደ ሰው እንዳይደለ አሳውቃችኋለሁ” (ገላ. 1፡11) ሲል ጽፏል።
የእግዚአብሔርን መገለጥ በዘመናት ከፍለን ካየነው በሦስት ዘመናት ከፍሎ መመልከት ይቻላል፡፡ የመጀመርያው ከመጀመርያው ሰው አዳም እስከ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ድረስ ያለውን በሕገ ልቡና በቃል፣ በራእይ፣ በተዓምር እየተገለጠ በማነጋገር አምላክነቱን አስረድቷል። (ዘፍ.2፥8-18፣ ዘፍ.3፥9፣ ዘፍ.12፥1) ሌላው ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እስከ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት ያለውን የሕገ ኦሪት ዘመንም በቃል በራእይ በተአምር እና ሕግና ሥርዓት በመስጠት አምላክነቱን አስረድቷል(አስተምሯል)። (ዘኁ 12፥5) በበሕገ ልቦናም ኦሪትም የነበሩት መገለጦች ምሳሌያዊ መገለጦች ሲሆኑ በሕገ ኦሪት ዘመን የእግዚአብሔር መገለጥ ከሕገ ልቡናው ዘመን ለየት የሚያደርገው በሕግና በሥርዓት ለእስራኤል መገለጡ ነው። የእግዚአብሔር ፍጹም መገለጥ ብለን የምንጠራው ዘመኑ ሲደርስ ለአዳም በገባው ቃል መሠረት በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል መገለጡን ነው። (ዕብ 1፥2)
እግዚአብሔር ራሱን የገለጠልን በምን መንገዶች ነው?
በፍጥረቱ እግዚአብሔር ይገለጣል
እግዚአብሔር በፍጥረት በኩል ራሱን ገልጦልናል። ፍጥረት “የእግዚአብሔር መገለጫ ናቸው” የሚንቀሳቀሱ ነገሮች የመጨረሻ ግባቸው ወደ ዘለዓለማዊ እና መልካም ህልውና መድረስ ነው። ፍጥረታት ማለት በሥላሴ መለኮታዊ የባሕርይ አንድነት በኃልዩ(በማሰብ)፣ በነቢብ(በመናገር) አልያም በገቢር(በመሥራት) የተፈጠሩ(ወደ ሕልውና የመጡ) የእግዚአብሔርን ባሕርይና አምላክነት የምንመለከትባቸው የሥራ ውጤቶች ናቸው። እግዚአብሔር አምላካዊ ሐሳብ ፍቃድ እቅድ ዓላማ አለው፤ይህንን ሰው አያውቅም። እግዚአብሔር ከሰው አእምሮ በላይ ነውና። ይህንን የእግዚአብሔርን ባሕርያዊ ሐሳብ ፍቃድና ዓላማ ዓለምን የፈጠረበት ምክንያት በፍጥረት ውስጥ በሚገባ እንረዳለን ከፈጠረው ፍጥረት በመነሳት የእግዚአብሔር ባሕርይ እንዲህ ነው እንላለን ምንም እንኳን ውስን በሆነው አእምሮችን የእግዚአብሔር ባሕርይ እንዲህ ነው ብለን በድፍረት መናገር ባንችለም እስካሁን ያወቅነውን ያወቅነው ከመገለጡ የተናሳ እንደሆነ ማስተዋል እንችላለን።
ስለዚህም እግዚአብሔር በፍጥረቱ ለፍጥረቱ ይታወቃል። ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ እንዳለ "ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ታይቶ የማይታወቅ እግዚአብሔር የፈጠረውን ፍጥረት በማሰብ በመመርመር ይታወቃል"(ሮሜ 1፥20) ስለዚህም በእምነት ለሚያይ ሰው እግዚአብሔር በፍጥረታት በኩል መገለጡን ያያል። የእግዚአብሔርን ሥራ በማድነቅ ይመለከታል ስለዚህም በእርሱ ያምናል ሌላም ምልክት አያሻውም። ለአማኝ ቅዱስ ዳዊት እንዳለ "ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ የሰማይም ጠፈር የእጆቹን ሥራ ያወራል" (መዝ 18፥1) እንዳለ ባለንጹሕ አእምሮ በፍጥረታት ውስጥ የእግዚአብሔርን ሕልውና(መኖር) ብቻ ሳይሆን፤ የእግዚብሔርን ባሕርይ ጨምሮ ወደመረዳት ይደርሳል ከግብሩ(ከሥራው) በመነሳት እግዚአብሔር እንዲህ ነው ይላል። የእግዚአብሔርን ለጋስነት፣ ያለስስት ሰጭነት፣ ጠባቂነት፣አዋቂነት፣ ከሃሊነት ወዘተ መመልከት ይችላል።
እግዚአብሔርን በፍጥረታቱ ስናውቅ የምናደንቀው በመፍጠሩ ብቻ አይደለም የፈጠረውን ፈጥሮ ብቻ አልተዋቸውም ዘወትር ይጠብቃቸዋል ይንከባከባቸዋል ይመግባቸዋል። ስለዚህም አምላክ ሰራዒ መጋቢ ጠባቂ መሆኑን እናውቃለን ባሕርይውን በጥቂቱ እንረዳለን። እግዚአብሔር መጠነኛ ባሕርይውን ብቻም ሳይሆን ልዩ ሦስትነቱን(ምሥጢረ ሥላሴን) ጭምር በፍጥረታት ገልጦልናል። ምንም እንኳን እግዚአብሔር በፍጥረታት በኩል ቢገለጥም ይህን መገለጥ የነገረ መለኮት ሊቃውንት ፍጹም ካልሆነው መገለጥ ይመድቡታል። ለዚህም ምክንያቱ መገለጡ በቀጥታ በራሱ ወደ ድኅነት የሚመራ ስላልሆነ ነው።
እግዚአብሔር ራሱን በቅዱሳት መጻሕፍት ይገለጣል
እግዚአብሔር ራሱን በቅዱሳት መጻሕፍት ማለትም በብሉይ ኪዳን (የእግዚአብሔር መገለጥ በተመረጡት የእስራኤል ሰዎች) እና በሐዲስ ኪዳን (የጌታችን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ መገለጥ) ገልጦልናል። በእርግጥም፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእውነት መዝሙረኛው አስቀድሞ “የተባረከ… በጌታ ስም የሚመጣው” የተባለለት ነው።
እግዚአብሔር ምጡቅ ረቂቅ ከአእምሮ በላይ ቢሆንም ከአባታችን አዳም ጀምሮ በተለያየ ጊዜ ለቅዱሳን ተገልጦል፡፡ (ዘፍ 3፥8) ሊቀ ነቢያት ሙሴ እግዚአብሔርን አምስት መቶ ሰባ ጊዜ ያህል አናግሮታል ተገልጦለታልም( ዘኁ 12፥5 )ለቅዱሳኑም ለሄኖክ መዓዛ ባለው እንጨት ለአብርሃም በሦስት ሰዎች አምሳል ለኖኅ በቀስተ ደመና ለያዕቆብ በመሳላል ከፍታ ላይ ተቀምጦ ለኢሳይያስ በዙፍኑ ተቀምጦ ለዕዝራ በአንበሳ አምሳል ለዳንኤል በሽበታም ሰው አምሳል ተገልጦል፡፡ ለነቢያቱም በብዙ ምሳሌ መገለጡም የእግዚአብሔርን የተለያየ ባሕርይ የሚያስረዳ ነው፡፡ በሸመገለ ሰው አምሳል ሲገለጥ ፍትሐዊነቱን፤ ብርቱ ጦረኛ ሲሆን ተዋጊነቱን፤ አንድ ቦታ እንዳጣ ነዳይ መታየቱን በአንድ ቦታ እንደሚዘገይ በሌላ ቦታ የሚቀድመው እንደሌለ መጻፉን አስተውል የባሕርያቱ ጥልቅነትን በመገለጡ እንደሚያስረዳን እናስተውላለን፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም እንዳለ ‹‹እርሱ እንደ መራዳችን መጠን ተገለጠ(አስተማረን) ስንል እርሱ ራሱ እንደኛ ነው ማለታችን አይደለም፡፡ እርሱ በእኛ ምሳሌ ተገለጠ ወይም አልተገለጠ እርሱ ራሱ ነው አይለወጥም፡፡ ሲፈልግ እኛን ለማስተማር አንዱ ጠባያችን ተገልጦ ይታየናል ሌላ ጊዜ ደግሞ አስቀድሞ የለበሰውን እንደልብስ አውልቆ ሌላ ልብስ ለብሶ ይገለጥልናል እርሱ ለእኛ በመንገሩ እርሱ እንዲህ ነው ማለት አይደለም ነገር ግን ባሕርይው የማይመረመር ነውና በምንረዳው በእኛ ምሳሌ ተገኝቶ ፍቃዱን ገለጠልን›› ለዚህም ነው ይህንን መገለጥ ምሳሌያዊ የምንለው።
ይህ መገለጡ የኩነት መገለጥ አይደለም። ልክ በፍጥረቱ በኩል በጥቂቱ እዳወቅነው በጥቂቱ ደግሞ ስለእርሱ እንደአእምሮችን መጠን እንደቅድስናችን ከባሕርይው በጥቂቱ እንድንረዳ የሚገለጥበት መንገድ ነው። ለነቢያቱም በሕልም በራዕይ ይገለጥ ነበር። ይህም መገለጥ ምንም እንኳን ራሱ እግዚአብሔር በተለያየ ምሳሌያዊ መንገድ ቢገለጥ ከድኅነት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ስለሌለው ፍጹም አይደለም። ባሕርይውንም አንድንረዳ ያግዘናል እንጂ የኩነት አይደለም። ለዚህም ነው ነቢያቱ ምንም እንኳን ለእነርሱ ምሳሌያዊ በሆነ መንገድ ቢገለጥም በሥጋ ይወለድ ዘንድ ሲናፍቁ የኖሩት በሥጋ መገለጡ ለድኅነታቸው አስፈላጊ ስለነበረ በጾም በጸሎት በተስፋ የእግዚአብሔርን መገለጥ ሲጠባበቁ ኖረዋል።
እግዚአብሔር ለተወሰኑ ሰዎች ስለራሱ የሰጣቸው መገለጦች ብዙውን ጊዜ የሚፈጸሙት ባልተለመዱ መንገዶች ወይም ከተፈጥሮ በላይ በሆነ መንገድ ነው። እግዚአብሔር ራሱን የሚገልጠው በራሱ ወይም በመላእክቱ ነው። እንዲህ ዓይነቱ መገለጥ ከተፈጥሮ በላይ የሆነ መለኮታዊ መገለጥ ይባላል።
ሁሉም ሰዎች ከራሱ ከእግዚአብሔር መገለጥን መቀበል እንደማይችሉ፣ በኃጢአት ርኩሰት እና በነፍስ እና በሥጋ ድካም ምክንያት፣ ጌታ ይህንን መገለጥ ሊቀበሉ የሚችሉ ልዩ ጻድቃንን ይመርጣል። የእግዚአብሔርን መገለጥ ካወጁት የመጀመሪያዎቹ ሰዎች መካከል አዳም፣ ኖኅ፣ ሙሴ እና ሌሎች ነቢያትና ጻድቃን ይገኙበታል። ሁሉንም ነገር ከእግዚአብሔር ተቀብለው የመለኮታዊ መገለጥን ጅማሬ ሰብከዋል።
በመለኮታዊ መገለጥ ፍጻሜ፣ እግዚአብሔር ራሱ በእግዚአብሔር ልጅ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ ለብሶ ወደ ምድር መጣ እና በሐዋርያቱ እና በደቀ መዛሙርቱ አማካይነት መገለጡን ወደ ምድር ሁሉ አሰራጨ። ይህ መለኮታዊ መገለጥ እና በሰዎች መካከል መሰራጨቱ በእውነተኛይቱ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን በሁለት መንገድ ተጠብቆ ይገኛል፡ በቅዱስ ትውፊት እና በቅዱሳት መጻሕፍት።
የመለኮታዊ መገለጥ ዋና መንገዶች ቅዱስ ትውፊት ነው። ከዓለም መጀመሪያ ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ቅዱሳት መጻሕፍት አልነበሩም። በእግዚአብሔር ማመንን ማስተማር በትውፊት ማለትም በአፍና በአርአያነት ከአንዱ ወደ ሌላው ከቅድመ አያት ወደ ዘር ይተላለፍ ነበር። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ መለኮታዊ ትምህርቱንና ትእዛዙን ለደቀ መዛሙርቱ ያስተላለፈው በአፍ፣ በስብከት እና በህይወቱ ምሳሌ እንጂ በመጻሕፍት (በቅዱሳት መጻሕፍት) አይደለም። በስብከትና ምሳሌነት፣ ሐዋርያት በመጀመሪያ እምነትን አስፋፍተው የክርስቲያን ቤተ ክርስቲያንን ጠብቀዋል።
ቅዱስ ትውፊት ሁል ጊዜ ከቅዱሳት መጻሕፍት ይቀድማል። ይህ ግልጽ ነው ምክንያቱም መጽሐፍት ለሁሉም ሰው የማይጠቅም ሊሆን ይችላል ነገር ግን ትውፊት ያለ ልዩነት ለሁሉም ተደራሽ ነውና።
እግዚአብሔር ራሱን ዛሬም ይገልጣል
እግዚአብሔር በዘመናት ሁሉ በቅዱሳን ሕይወት፣ በቤተ ክርስቲያን አባቶች ጥበብና ማስተዋል፣ በመለኮታዊ ሥርዓት እና በኦርቶዶክስ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ምሥጢር ሁሉ ራሱን ገልጦልናል።የክርስቶስን መገለጥ የምትሰብከውም ክርስትና የመገለጥ ሃይማኖት(Revealed religion) ናት መባልዋ ለዚህ ነው፡፡
እግዚአብሔር በራሳችን ሕይወትም ራሱን ሊገልጥልን ይችላል። እግዚአብሔር ራሱን እንዲገልጥ ከፈለግን፣ አእምሮአችንን እና ልባችንን ማጥራት እና እግዚአብሔር ለሚሠራበት ቦታ ራሳችንን ዝቅ ማድረግ አለብን። አንድ ኦርቶዶክሳዊ አባት እንዲህ ይላል፡- "እግዚአብሔር ለሁሉም ፍጥረት ምሥጢር ነው… እርሱ በሁሉም ቦታ ይገኛል… ራሱን ነገር ግን የሚገልጠው ለትሑታን እና ለትሑታን ብቻ ነው።" በዚህ መንገድ እራሱን ከገለጠልን እና ለሚወደው እራሱን ከሚገልጠው ከእግዚአብሔር ጋር ሕያው ኅብረት ሊኖረን ይገባል። ለዚህም የቅዱሳኑ ጸሎት ይርዳን።