Thursday, 30 May 2024

ኦርቶዶክሳዊ የንስሐ ሕይወት (ክፍል ሁለት)

በዲያቆን ያሬድ መለሰ

ለአስታየትዎ ymelese04@gmail.comን ይጠቀሙ

ውድ ኦርቶዶክሳዊያን በክፍል አንድ የንስሐን ምንነት ከኃጢአት ትርጉም በመነሳት ለማየት ሞክረናል በክፍል ሁለት የንስሐ ሦስቱ ደረጃዎች የንስሐ ጥቅም(አስፈላጊነትን) በተመለከተ በጥቂቱ እንላለን፡፡ መልካም ንባብ

ሦስቱ የንስሐ ደረጃዎች

ንስሐ የክርስትና ማዕከላዊ ጭብጥ ነው። “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!” የሚለው ትምህርት ወደ ጌታ እንዲመጡ ለመዘጋጀት አስቀድሞ የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት ያስተማረው ትምህርት ነው ከዚህም በተጨማሪ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስም ትምህርት መነሻ ነው። (ማቴ 3፡2፣ ማቴ 4፡17) እንግዲህ ንስሐ በእውነት በክርስቶስ የሕይወት መጀመሪያ ነው።

 

ንስሐን በሦስት ደረጃዎች በመክፈል መመልከት ያሻል፡፡

1.   ጸጸት

ለድርጊታችን የሚሰማን የጸጸት እና የኃዘን ስሜት፤ በተለይ በእንባ ታጅቦ ለነፍሳችን መዳን የመጀመሪያ እርምጃ ነው። ቁስላችን መክፈትና እውነተኛ መድኃኒት መሻት ነው፡፡ ከዚህ ውጭ ግን ማድረግ ቁስሉ እየጠነከረና እየተስፋፋ ትልቅ ጉዳት ሊያደርስብን ይችላል።

ሆኖም፣ ጥሩ ጅምር ቢሆንም፣ መጸጸቱ ብቻ በቂ አይደለም። ይሁዳ ጌታችንን ከዳ በኋላ በድርጊቱ አዘነ። በጣም አዝኖ የደም ገንዘቡን መልሶ ወጣና ራሱን ሰቀለ። ኃዘኑ እዚያ ቆመ ወደ ንስሐም አላበበም። ጴጥሮስም ወድቆ አዝኖ ነበር፣ ነገር ግን በዚህ ብቻ አላቆመም። ወደ ክርስቶስ ተመለሰ።

2.   ለመመለስ ውሳኔ

ለመመለስ መወሰን የንስሐ ዋና አካል ነው። በአባካኙ ልጅ ምሳሌ፣ “ወደ ራሱ ተመለሰ” በሚለው አገላለጽ ይገለጻል (ሉቃ. 15፡17) ይህም ማለት ወደ ልቡ ተመልሶ ምን ያህል እንደወደቀ ተገነዘበ። የአባቱን ቤት ውበት ያስታውሳል ለራሱ አያመካኝም። ለደረሰበት ችግር አባቱን ወይም ሌላን አይወቅስም። እርሱ ራሱ የውድቀቱ ደራሲ መሆኑን ተቀብሎ ወደ አባቱ ቤት ገሰገሰ።

 


ንስሐ ለመግባት እውነተኛ ድፍረት እንደሚያስፈልግ ምንም ጥርጥር የለውም፣ ኃጢአት ለመሥራት የደፈርነውን ያህል ንስሐ ለመግባት (ኃጢአትን ለማመንና ለመናዘዝ) ድፍረት ያስፈልጋል። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፡- “ንስሐ በገባህ ጊዜ ሳይሆን ኃጢአት በሠራህ ጊዜ እፈር አስተውል ሰይጣን ለኃጢአት ድፍረትን ለንስሐም ነውርን ይሰጣል።” ያለው ለዚህ ነው፡፡

3.   ድርጊቶች - የንስሐ ፍሬዎች

ለመለወጥና የቀድሞ አኗኗራችንን ለመተው የምናደርገው ውሳኔ የአእምሮ እንቅስቃሴ ብቻ ሳይሆን እውን እንዲሆን በተግባር ልንተገብረው ይገባል። ዳግም መውደቅን ለማስወገድ ትግል መደረግ አለበት። በአባካኙ ልጅ ምሳሌ ውስጥ፣ ከዚያ ባዕድ አገር ወደ አባቱ ቤት መመለሱ ለዚህ ምሳሌ ነው።

ለእኛ ኦርቶዶክሳውያን ንስሐ መግባት የአንድ ጊዜ ክስተት ሳይሆን የሕይወት መንገድ ነው። ኃጢአተኞች ስለሆንንና እስከ ምድራዊ ሕይወታችን ፍጻሜ ድረስ ኃጢአተኞች መሆናችንን እንቀጥላለን፣ በንስሐ ሁኔታ ውስጥ እንድንኖር ተጠርተናል። ቤተክርስቲያን እንዲህ ትጸልያለች ዘኀለፈ ሥርየት ወዘበይመጽእ ዕቅበት …

የንስሐ ጥቅም

ያለንስሐ ድኅነት የለም፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ንስሐ ባትገቡ ኹላችሁ እንዲሁ ትጠፋላችሁ›› ብሏል (ሉቃ 13፥3) ‹‹እንኪያስ እግዚአብሔር ለአእዛብ ደግሞ ለሕይወት የሚሆን ንስሐ ሰጣቸው›› (ሐዋ 11፥18) ‹‹በኃጢያታችን ብንናዘዝ ኃጢያታችንን ይቅር ሊለን ከአምጻም ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው፡፡››ይላል (1ኛ ዮሐ 1፥7-9) ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹ንስሐ ግቡ ኃጢያታችኹም ይሰረይ ዘንድ›› ብሎናልና (ሐዋ 2፥38) ስለዚህም ንስሐ ከጥፋት ለመዳን የኃጢአት ሥርየት አግኝቶ እግዚአብሔርን ለመምሰል አስፈላጊ ነው፡፡

ይቆየን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

 

No comments:

Post a Comment