Tuesday, 9 July 2024

የክርስቶስ ሙሽራ ቤተ ክርስቲያን(ክፍል አንድ)

በዲያቆን ያሬድ መለሰ

ለአስታየትዎ betehawariat@gmail.comን ይጠቀሙ


መግቢያ

ህ ዘመን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በተመለከተ የተዛቡ አስተሳሰቦችና አመለካከቶች የሚንጸባረቁበት ዘመን ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ “ሰዎች እኔ ማን እንደ ሆንሁ ይላሉ?” (ማቴ. 16፥13) ብሎ የጠየቀውን ጥያቄ በርግጥ ዛሬ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን “ሰዎች ቤተ ክርስቲያንን ማን እንደሆነች ይላሉ?” ብለን መጠየቅ የሚገባን ዘመን ነው። ዛሬ ዛሬ ሰዎች "በክርስቶስ እናምናለን" ይላሉ ግን ቤተ ክርስቲያንን “መልክና ውበት እንደሌላት” (ኢሳ. 53፥2) በሰው ልጆች ድኅነት ላይ ምንም ድርሻ እንደሌላት አንዲት ተቋም አድርገው የሚመለከቱ ብዙዎች አሉ። በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ስለቤተክርስቲያን የምናገኘው ዋና ምስል ግን ከዚህ በእጅጉ ይለያል።በዚህ ጽሑፍ ይህን በቅዱሳት መጻሕፍት የተገለጠውን የቤተ ክርስቲያንን ምስል ለማየት እንሞክራለን።ለዛሬ በባልና በሚስት መካከል ባለው ግንኙነት የተመሰለውን የክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን አንድነት እንመለከታለን።

ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው (ኤፌ.5፥22-32)

በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ የምናገኘው የቤተክርስቲያን ዋና ምስል ቤተክርስቲያን የክርስቶስ ሙሽራ(ኤፌ.5፥22-32) እንደሆነች ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የክርስቶስንና የቤተ ክርስቲያንን ግንኙነት በተመለከተ በባልና በሚስት መካከል ባለው ግንኙነት መስሎን አስተምሮናል። ክርስቲያኖች ወደ መዳኑ ይቀርቡ ዘንድ የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች የሚሆኑባት (2ኛ ጴጥ. 1፥4) ቤተ ክርስቲያን ናት። ደራሲው እንዳለ በእውነት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሰው ልጆች መድኃኒትና እስከዘለዓለም ገዥ ናት። 

የክርስቶስ አካልና ሙሽራ-ቤተ ክርስቲያን

የጋብቻ ወሳኝ ሀሳብ ከብዙነት አንድነትን መፍጠር ነው። ባልና ሚስት "አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ወደ ፊት ሁለት አይደሉም" (ማቴ. 19፥6) እንዳለን በቅዱስ ጋብቻ አንድነትን ይመሠርታሉ። በቤተክርስቲያኑ ውስጥ ይህ አንድነት በክርስቶስና በእያንዳንዱ አማኝ መካከል እንዲሁም በክርስቶስና በአማኖች መካከል ያለ ኅብረት ነው። የኅብረቱ መሠረትና አብነት በትምህርተ ሥላሴ እንደተማርነው በሦስቱ አካላት መካከል ያለው አንድነት የመሰለ ነው።  ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው ስለ ቤተ ክርስቲያን አንድነት እንደጸለየ "ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ…. አንተ አባት በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ…...እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ (ዮሐ. 17፥21-22) ።

ይህንን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ወቅት የጸለየውን ጸሎት በቅድስት ሥላሴ መካከል የተገለጸው ኅብረትና አንድነትን የመሰለ አንድነትና ኅብረትን ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጣት ዘወትር ትለምናለች። በቅዳሴያችን "ወበከመ አስተጋባእካ ለዛቲ ኅብስት እንዘ ዝሩት ይእቲ ወስተ አድባር ወአውግር ወተጋቢኣ ኮነት አሐተ ኅብስተ ፍጽምተ ወከማሁ ኪያነሂ አስተጋብአነ በመለኮትከ እምኩሉ ሕሊና እኩይ ውስተ ሃይማኖትከ ፍጽምት…" "ይህችን ኅብስት በተራራና በኮረብታ የተበተነች ስትሆን እንደ ሰበሰብካት ተሰብስባትም አንዲትም ፍጽምት ኅብስት እንደሆነች እንዲሁም እኛን በጌትነትህ ከክፉሕሊና ሁሉ ለይተህ በሃይማኖት አንድ አድርገን…."(ቅዳሴ ጎርጎርዮስ ካልዕ) ማለታችንም ይህንን የሚያመላክት ነው። ዳግመኛም « በኵሉ፡ ልብ፡ ናስተብቍዖ፡ ለእግዚአብሔር፡ አምላክነ፡ ኅብረተ፡ መንፈስ ቅዱስ፡ ሠናየ፡ ከመ፡ ይጸግወነ። በፍጹም ልብ አምላካችንን እግዚአብሔርን እንለምነው፥ ያማረ የመንፈስ ቅዱስን አንድነት ይስጠን ዘንድ» በማለት ዲያቆኑ በቅዳሴ ጊዜ የሚያሳስበንም ለዚህ ነው። 


ቤተክርስቲያን የሥላሴ ፍጹም አንድነት ነጸብራቅ ናት። በዚህ የጸሎት ክፍል ውስጥ የክርስትና ምንነት በግልጽ ተቀምጧል። ክርስትና በአእምሮ የሚቀበለውና በእያንዳንዱ ሰው ተለይቶ የሚገኝ ረቂቅ ትምህርት አይደለም። ነገር ግን ክርስትና የተለያዩ አካላት እርስ በርሳቸው የተዋሐዱበት አንድነታቸው ከቅድስት ሥላሴ አካላት አንድነት ጋር የሚመሳሰልበት ሕይወት ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው የጸለየው ጸሎት ትምህርቱ ተጠብቆ እንዲቆይ ብቻ ሳይሆን ትምህርቱ በመላው ዓለም ሁሉ እንዲሰራጭ ነው። በእርሱ ለሚያምኑት ሁሉ አንድነት ጸለየ። ቅዱስ ጳውሎስ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከአንድ ፈጠረ (ሐዋ. 17፡26) እንዳለ የሰው ልጆች ሁሉ የተፈጥሮ አንድነት እንዲመሠረት፣በትክክል ወደቀደመ ማንነቱ እንዲታደስ ወደ ሰማያዊ አባቱ ጸለየ።

ቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ በተመለከተ ሲናገር “ክርስቶስ የባሕርዩ ምሳሌ (ዕብ. 1፥3) የማይከፋፈል ፍቅርን፣ መስማማትንና አንድነትን ከእርሱ ጋራ በአንድነት ብቻ የሚታሰብ አብ ከእርሱ ጋር ያለውን አንድነትና ምሳሌ አድርጎ በመውሰድ እርሱ ደግሞ ከአብ ጋር ያለው፣ እኛ ደግሞ እርስ በርሳችን እንዲኖረን እንደሚፈልግ ያመለክታል። ቅድስት ሥላሴ አንድ በመሆን መላው የቤተ ክርስቲያን አካል እንዲጸነስ በክርስቶስ አማካኝነት የአማኞች ውህደትም ወደ አዲሱ ፍጹም አንድነትና ኅብረት ይለወጣል። የቅድስት ሥላሴ ፍጹም መስተጋብር አንድ ልብ በሆኑ አማኞች አንድነት በአእምሮ በልብና በአካል ውስጥ መንጸባረቅ አለበት። ይህም አንድነት ሥጋዊ አንድነት አይደለም" ብሏል።

በክርስቲያናዊ ጋብቻ በአንድ ሥጋ ውስጥ ያለውን አንድነት የሚያመለክት ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉ አማኞች ሁሉ የአንድነት አምሳል ነው። ይህም ለትልቁ ማኅበር መሠረት፣ እንደዝቅተኛ ሕዋስ ያለ ነው።ቅዱስ ጳውሎስ "በቤታቸው ላለች ቤተ ክርስቲያን ሰላምታ አቅርቡልኝ።" እንዳለ (ሮሜ 16፡5) ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅምትንሿ ቤተ ክርስቲያን (little church)የሚለው ይህንን ነው። የክርስቲያን ቤተሰብ “የቤት ውስጥ ቤተክርስቲያንማለት ብቻ አይደለም። ቤተክርስቲያኑ ሁለቱም ከትናንሽ ቤተሰቦች ወይም ከትናንሽ አብያተ ክርስቲያናት የተዋቀረች በክርስቶስ ስም የተሰየመችበሰማይና በምድር ያለ ቤተሰብ በሙሉ” ያቀፈች (ኤፌ. 3፥15) አንድ ትልቅ ቤተሰብ ወይም ታላቅ ቤተክርስቲያን ናት።

ይቆየን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

Saturday, 6 July 2024

ኦርቶዶክሳዊ የንስሐ ሕይወት (ክፍል አምስት)

በዲያቆን ያሬድ መለሰ

ለአስታየትዎ ymelese04@gmail.comን ይጠቀሙ

ውድ ኦርቶዶክሳዊያን በክፍል አራት ንስሐና ኃጢአትን መናዘዝ(ኑዛዜ)የካህናት ድርሻ በንስሐና በኑዛዜ፣የክህነት ፀጋ የንስሐ አባትና የንስሐ ልጅ ግንኙነት በተመለከተ ለማየት ሞክረናል በዚህ ክፍል ቀኖና ለምን ይሰጣል? የኑዛዜ ጥቅም እንዴት መናዘዝ እንደሚገባ በተመለከተ በጥቂቱ እንላለን፡፡ መልካም ንባብ

ቀኖና ለምን ይሰጣል?

 ቀኖና እንደ ቅጣት ዓይነት መታሰብ የለበትም። ተፈጥሯዊው ሕሊናም ወቃሽም አስተማሪም ነው። ቀኖና የሚሰጠው የተበሳጨውን እግዚአብሔርን ለማስደሰትና በመለኮታዊ ፍትህ ፊት ለኃጢአተኛው ሥርየት ሲባል አይደለም። ይህ ሙሉ በሙሉ የመናፍቃን ትምህርት ነው። ቀኖና አብዛኛውን ጊዜ የሚተገበረው ያልበሰለ የኑዛዜ ሕይወት ላለው ተነሣኢ ሊሆን ይገባዋል። ይህም ግንዛቤን ለመቀስቀስና የአንድን ሰው የኃጢአት መጠን ለማወቅ በማሰብ ነው። በኦርቶዶክሳዊ አረዳድ መሠረት "ኃጢአት" ማለት ሕግን መተላለፍ አይደለም። ለእግዚአብሔር ፍቅር ማጣት ነው። ንስሐም ካሣ አይደለም።ስለዚህም ይህንን በመንፈሳዊ ልምምድ ወደ ፍጹም ንስሐና ወደ እግዚአብሔር ፍቅር ማድረስን ከመንፈሳዊ አባት ይጠበቃል።

ካህኑ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ሰጪ ሆኖ ይሠራል። እንደ ሳይኮሎጂስትና ሳይንቲስት አይሰራም እንደ ካህን፣ እንደ ልምድ ያለው ዶክተር፣ እንደ አሳቢ አባት ሆኖ ይሰራል። የተናዘዘውን ሰው ኃጢአት በሚያዳምጥበት ጊዜ አምላክ ብርሃን እንዲሰጠው፣ ከሁሉ የተሻለው መድኃኒት ምን እንደሆነ እንዲያመላክታለው እንዲሁም የኑዛዜውን ደረጃና ጥራት እንዲገልጽለት ይጸልይ ዘንድ ይገባል።

ራሱን ከተናዘዘ ሰው ጋር በጉጉት፣ በጥርጣሬ፣ በምቀኝነት፣ ከመጠን ያለፈ ቁጥብነት፣ ኃይልና እብሪተኝነት አያስቀምጥም። ግን በተመሳሳይ ሁኔታ በግዴለሽነትና በድካም አይደለም። የተናዛዡ ትኅትና፣ ፍቅርና ትኩረት የሚናዘዙትን ሰው በእጅጉ ይረዳል።


 

የኑዛዜ ጥቅም

ቅድስት እናታችን ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የትንሣኤው የክርስቶስ አካል ናት። እሷ ደካሞችን ለመፈወስ ሰፊ ማቆያ ናት። የቁስሎችን፣ የድዉያንንና የኃጢአት በሽታዎችን ትፈውሳለች(ማቴ.9፥10-12)። በሽታ አምጪ አጋንንት፣ከመርዛማ የአጋንንት ወጥመዶች፣በአጋንንት የሚነዱ ስሜቶችና ተጽእኖዎች ማረፍያችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት። (ለውሉደ ሰብእ መድኃኒት ወእስከ ለዓለም ሰፋኒት የምንለው ለዚህ ነው)

ቤተ ክርስቲያናችን የማኅበራዊ አገልግሎት ተቋም አይደለችም። ነገር ግን ቤተክርስቲያን በዋነኛነት የሕይወት ትርጉም፣ ለዓለም ቤዛ የሆነው የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አማናዊ ሥጋና ደም የሚፈተትባት የምእመናን ቤዛ እና ድኅነት አቅራቢ ነች።

እግዚአብሔር ካህኑን ለፍጡራን ይቅርታ ይጠቀምበታል። በኑዛዜ ቃሉ ‹‹ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የካህናት አለቃ ለአባቶቻችን ለቅዱሳን ሐዋርያት ሥልጣነ ክህነትን የሰጣቸው ከልጅነት እስከ እውቀት የሠራችሁትን ይቅር ይበል…እምማዕሰረ ኃጢአት እግዚአብሔር ይፍታ›› ብሎ ከእስራት መፍታትና ለፍጡራን ይቅርታ ስልጣንን ሰጥቶታል። ለዚህም ነው ካህኑ በጸሎተ ኪዳን ‹‹ከመ እምሰብእ ይኩኑ አማልክተ…… ከመ ንፍታሕ ዘኢይትፈታሕ ፍቅረ ለነ ኀበ አቡከ ገበርከ ለነ›› የማይፈታውን እንፈታ ዘንድ ከአባትህ ዘንድ ፍቅርን አደረክልን የሚለው።

እንዴት መናዘዝ እንደሚገባ

የተናዘዝናቸውን ኃጢአቶች እንደገና እንናዘዛቸው ዘንድ አይገባም። ይህ በኑዛዜ የምናገኘውን ፍጹም ይቅርታና ምሕረት እንደመጠራር ይቆጠራል። አንድ ሰው እግዚአብሔር የምንሠራውን ኃጢአትና በደል ካወቀ ለምን መናዘዝ ያስፈልገኛል ሊል ይችላል። በእርግጥም እግዚአብሔር ሁሉን ያውቃል ነገር ግን ራስን ለማዋረድ(ለትኅትና) መናዘዝ ያስፈልጋል። ዳግመኛም በደሉና ኃጢአቱን ዳግም እንዳይሰራ አስተማሪ የሆነ ጫና መሆኑን መገንዘብ አለበት።

አንድ ኦርቶዶክሳዊ አባት እንደገለጸው፣ ኑዛዜ ማለት የአንድን ሰው የሰራውን ክፉ ሥራ፣ ቃላቶች እና ሐሳቦች በፈቃደኝነት፣ በቃላት መግለጥ ነው። ለእግዚአብሔር ያለን እውነተኛ አክብሮት መገለጫ መጸጸትን፣ ኃጢአትን መጥላትን፣ በጎነትን መውደድና ለስጦታ ሰጪው አምላክ በማመስገን ነው።

አንድ ሰው ሽንፈቱን፣ ውድቀቱንና ድክመቱን አምኖ ለመቀበል ይቸገራል።ለሠራነው ኃጢአት ሌሎችን መክሰስ ምክንያት መደርደር የመሳሰለውን በእጅጉ ማስወገድ ያስፈልጋል።ኀፍረት ከኃጢያት በፊት መኖሩ ጥሩ ነገር ነው ከዚያም በኋላ አይደለም። ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ እንዳለው ንስሐ በገባህ ጊዜ ሳይሆን ኃጢአት በሠራህ ጊዜ እፈር። ሰይጣን የሚያዛባው ቅደም ተከተሉን ነው ኃጢአት ስንሰራ እንዳናፍር ንስሐ ስንገባ እንዳንናዘዘው በማሳፈር ያስተናል። ኀፍረት በመጨረሻው ፍርድ ከኃጢአታችን ነጻ ያደርገናል ተብሏል፡ ምክንያቱም ተናዛዡ የሚፈታው ሁሉ ዳግመኛ አይፈረድበትም።

በተጨማሪም ኑዛዜ ቀጣይነት ያለው መሆን አለበት፣ ስለዚህም "በሆን ብለው የሚደጋገሙ" ስሜቶች (እንደ ባለመሰላሉ ቅዱስ ዮሐንስ ገለጻ) እንዳይጠናከሩ፣ ይልቁንም በፍጥነት እንዲድኑ ያግዘናል። ስለዚህ በቋሚነት እራስን መከታተል ራስን መመርመር በእጅጉ ያስፈልጋል።ለዚሀም እግዚአብሔር ይርዳን።

ይቆየን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር